በዩኒቨርሲቲው የተወሰኑ ግቢዎች ተቋርጦ የነበረው መማር ማስተማር ጥር 1 እና 2/2011 ዓ.ም ይቀጥላል

ታህሳስ 30/2011 ዓ.ም

በዩኒቨርሲቲው የተወሰኑ ግቢዎች ተቋርጦ የነበረው መማር ማስተማር ጥር 1 እና 2/2011 ዓ.ም ይቀጥላል

በቅርቡ በአንዳንድ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተፈጥረው በነበሩ አለመረጋጋቶች ምክንያት በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የተወሰኑ ግቢዎች ተቋርጦ የነበረው መማር ማስተማር ሂደት ነገ ጥር 1/2011 ዓ.ም ይቀጥላል፡፡

በነዚህ አለመረጋጋቶች ምክንያት በዩኒቨርሰቲው አንዳንድ ግቢዎች ተቋርጦ የነበረው መማር ማስተማር ነገ (ጥር 1/2011 ዓ.ም) የሚቀጥለው የዩኒቨርሲቲው ሴኔት በወሰነው መሰረት ነው፡፡ ሴኔቱ ተማሪዎች በተጠቀሰው ጊዜ በትምህርት ገበታቸው ላይ ተገኝተው ትምህርታቸውን እንዲቀጥሉ ከመወሰኑ ጎን ለጎን የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብና የአካባቢው ማህበረሰብ ተማሪዎች አሁንም ሰላማዊና ምቹ በሆነ የመማር ማስተማር ከባቢ ውስጥ ትምህርታቸውን እንዲቀጥሉ ለማድረግ የሚያስችሉ የተለያዩ ስራዎችን እየሰሩ ነው፡፡

በዚህም ትምህርታቸውን አቋርጠው የነበሩ ተማሪዎች ባልተረጋገጡ መረጃዎች መነሻነት በግቢዎች ውስጥም ሆነ ከውጭ ሊገጥሙን ይችላሉ በሚል ያደሩባቸው ስጋቶች ትክክል እንዳልሆኑ ይልቁንም የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ (መምህራን፣ ተማሪዎች፣ የአስተዳደር ሰራተኞችና አመራሮች) እንዲሁም የአካባቢው ማህበረሰብ (የከተማው አስተዳደር፣ ወጣቶችና የፀጥታ አካላት) በተለያዩ መድረኮች ውይይቶችን እያካሄዱ ለሰላማዊ መማር ማስተማሩ እንደቀድሞው የየበኩላቸውን አስተዋጽኦ ለማበርከት ዝግጁነታቸውን አረጋግጠዋል፡፡

ስለዚህ መደበኛው የመማር ማስተማር ሂደት በተወሰኑ ግቢዎች ያለምንም ችግር እንደቀጠለ እያለ በተወሰኑ ግቢዎች ትምህርት አቋርጠው የነበሩ ተማሪዎቻችን በተደረገው ጥሪ መሰረት ጥር 1 እና 2/2011 ዓ.ም በትምህርት ገበታቸው ተገኝተው በተለመደው አኳኋን ትምህርታቸውን እንዲቀጥሉ ለማድረግ ዩኒቨርሲቲው የበኩሉን ዝግጅት አጠናቋል፡፡  

ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ አገራችን በምታደርገው አወንታዊ የለውጥ ሂደት ውስጥ የበኩሉን የማይተካ ሚና የሚጫዎት የተማረ የሰው ሀይል ለማፍራት በሚያደርገው ያላሰለሰ ጥረት የሚያጋጥሙ ችግሮችን ለመፍታት ተማሪዎች በጋራ  ውይይቶች በመሳተፍ የመፍትሄ አካል መሆን ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ ዛሬ አስፈላጊ እንደሆነ መገንዘብ የሚኖርባቸው ሲሆን ተቋሙም ከተማሪዎች ጋር በጋራ በመስራት ሰላማዊ መማር ማስተማርን በማረጋገጥ ይህን ታላቅ የሀገር ሃላፊነት በብቃት መወጣት እንደሚቻልም በፅናት ያምናል፡፡

ባሕር ዳር ዩኒቨርሰቲ

Wednesday, January 9, 2019 - 08